Tag Archive for: ፖለቲካ

ወደ አምባገነናዊ ስርዓት መመለስ አገር ያሳጣል

ለዚህ  ጽሁፌ መነሻ ምክንያት ወደ ሆነኝ ነጥብ ልምጣና የኢህአዴግ አልጋ ወራሽ የሆነው ብልጽግና ልክ እንደትላንቱ ዛሬም በተመሳሳይ ጎዳና እየገሰገሰ ይገኛል። ኩንትራቱን ሊጨርስ እየተቃረበ ያለው ጠ/ሚ/ር አብይ አሕመድ፣ በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን ክፍፍል በአሸናፊነት ተወጥቶ ስልጣኑን ለማደላደል ሲል ብልጽግናን የመሰረተበት ሒደት፣ ድርጅቱን ለማጠናከርና አባላትን ለማፍራት እየተጓዘበትና ያለው መንገድ ከቀድሞ የኢህአዴግ ባህል ምንም የተለየ አይደለም። ኢህአዴግ የቀድሞ ስሙን ብቻ ቀይሮ በህይወት አለ። ልዩነቱ የቀድሞ ታጋዮች ኮትኩተው ባሳደጓቸው ካድሬዎች በፖለቲካ ጌም መሸነፋቸው ብቻ ነው። ሰዎቹ ተሸነፉ እንጂ የዘረጉት ባህል አልተሸነፈም። ካድሬዎቹ ከህወሓት ካድሬዎች ውጪ ቀሪዎቹ የነበሩት ናቸው። የሚተዳደሩት በለመዱትና በኖሩበት የድርጅት ባህል ብቻ ነው። ለዚህም ነው ብልጽግና ከኢህአዴግ የተለየ ባህል ሊኖረው የማይችለው።

ጠ/ሚ/ሩ በህዝብ ይሁንታ፣ በተሰጠው የሁለት አመት የስልጣን ገደብ ቀድሞ የገባውን ቃል አጥፎ፣ የዴሞክራሲ ተቋማትን ሳይገነባ፣ ነጻና ገለልተኛ ምርጫ ሳያካሒድ፣ ስልጣን በሰላማዊ መንገድ በህዝብ ለተመረጠ አሸናፊ ፓርቲ ማስተላለፍ የሚችልበትን እድል ሳይፈጥር፣ በማንኛውም መንገድ ስልጣን ላይ ለመቆየት የሚያስችሉትን አማራጮች እየዘረጋ ቆይቷል። አንዱ መንገድ የቀድሞ አጋሮቹን ገፍትሮ በአዲስና ታማኝ ካድሬዎች መተካት ነው። እኔ አሻግራችኋለው ከማለት ስልጣን ላይ ካልቆየሁ መታሰራችን ነው ወደ ማለት ተሸጋግሯል። ይህ አፍሪካ ነው፣ ምርጫ ማጭበርበር ብርቅ አይደለም ማለቱም ተሰምቷል። አንድ ሰሞን መተካከት የሚባል የፖለቲካ ዲስኩር ተፈጥሮ ነበረ። አቶ መለስ የቀድሞ ጓዶቹን በመተካካት አሰናብቶ፣ በአዲስ ሀይል ተካቸው። እኔም በቅቶኛል ስልጣን ለአዲሱ ትውልድ አስተላልፋለሁ ሲል ቆይቶ፣ ባለቀ ሰዓት ድርጅቴ መርጦ አዲስ አደራ ስለጣለብኝ፣ ግዴታዬን መወጣት አለብኝ አለ። በ99.96% አሸነፍኩ ብሎ የለየለት አምባገነን ሆኖ ብቅ አለ።

ዛሬም ዶ/ር አብይ እየተጓዘበት ያለው መንገድም ተመሳሳይ ነው። አሻግራለሁ ሲል ቆይቶ፣ ሌላ መሪ ማን አለ እስከማስባልና ዛሬ ስልጣን ላይ ካልቆየን መታሰራችን ነው የሚል አቋም እስከማራመድ ድረስ ዘልቋል።

ምርጫውን መራዘም አለበት የሚል ዘመቻ የተከፈተው አምና ነበር። ከተራዘመ የቅቡልነት ጥያቄ ሊነሳ እንደሚችል ሲገለጽ፣ ነሓሴ እንደሚካሔድ ተገለጸ። ውሳኔው ምርጫው በግፊት የሚራዘምበትን ሰበብ ለመፍጠር ያለመ ይመስል ነበር። የኮቪድ ወረርሽኝ ሲከሰት፣ ጥሩ አጋጣሚ ሆነለትና ምርጫው እንዲራዘም ተደረገ። ምርጫው መራዘሙ ብቻ ሳይሆን፣ ያልተገደበ ስልጣን የሚሰጠው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አሳወጀ። አዲስ የአፈና መርበብ ተዘረጋ። ስልጣን ላይ በጉልበት ለመቆየት ርብርቡ ቀጥሏል።

ይህ በዙርያው ላሰባሰባቸው ኪራይ ሰብሳቢዎች ትልቅ ሲሳይ ነው። ከህዝብ ተነጥሎ በካድሬና በድርጅቱ ሰዎት መተማመን ከጀመረ፣ መዝረፍ የፈለገ አሁን እንደልቡ ይዘርፋል። እንደድሮ በግፍ ራሱን ማዝናናት የሚያስፈልግ ካለም አሁን ያን ማድረግ ይችላል። ምክንያቱም ሰውዬው ከህዝብ ተነጥሏል። የሚፈራው ነገር እንዳይደርስበት ካድሬዎቹን ሸክፎ መያዝ አለበት። ሲሰርቁና ግፍ ሲፈጽሙ እየቀጣ ካድሬን ሸክፎ ማቆየት ደግሞ አይቻለውም። ስለሆነም ነጻ ይለቃቸው፣ ከቁጥጥሩ ውጭ ናቸው።

ትላንት በኮረና ስም፣ ትንሽ ሰብሰብ ያሉ ሰዎችን ለመበተን ሲባል፣ ወጣቶችን ገደሉ። እንደገና ቤት አፍርሰው ደግሞ በርካቶችን ለበሽታው ማጋለጣቸው አልቀረም። ከእንግዲህ እንዲህ አይነት ዝብርቅርቁ የወጣን ነገር ማስታረቅም፣ ማረምም አይቻለውም ጋሽ አጃግሬ። ያለው አማራጭ በስልጣኑ እስካልመጡበት ድረስ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ማለፍ ነው።

አብይ ብዙ ጊዜ ስቷል። አንኳር ስ ህተቶቹ ግ ን ሁለት ናቸው። አንደኛ ተቋማትን መገንባትና ራሳቸውን ችለው እንዲንቀሳቀሱ ማድረግ ሲገባው፣ እርሱን የሚያወድሱና በስልጣን ላይ ሊያቆዩት የሚሹ አጨብጫቢዎችን አፈራ። ሁለተኛ ስልጣን እየጣፈጠችው ስትሔድ ከህዝብ እየራቀ ሔደ፣ አምባገነናዊ ባህሪ እየተላበሰ ሔደ። አሁን መፍራት ጀመረ። ፍራቻው አገርን እንዳያሳጣን እፈራለሁ።

ሊበራላይዜሽን?መለስ ዜናዊ እና አብይ አሕመድ

መለስ ዜናዊን በብዙ ምክንያት እቃወመው ነበር። ይህን ከፋፋይ የዘር ፖለቲካ ማምጣቱ፣ ስልጣን ላይ ሙጭጭ ማለቱ፣ ስልጣን ላይ ለመቆየት የተጓዘበት ርቀት(የሚመራው ድርጅት በሀሳብ ድርቅ እስኪጠቃ ድረስ የተማረ ሰው የማያስጠጋ መሆኑ)፣ ወዘተ ሊጠቀሱ የሚችሉ ናቸው። ማንም የማይክደውና የሚደነቅበት ብቃት ደግሞ ነበረው። የኢኮኖሚክስ እውቀቱ ከባድ ሚዛን (ወርልድ ክላስ) ነበር።

መለስእነ ጆሴፍ ስቲግልዝ (በኢኮኖሚክስ ኖቤል ተሸላሚዎች) ፣ እነ ፒተር ጊልስ (አዋርድ ዊኒንግ ጋዜጠኞች)፣ እነ አሌክስ ዴ ቫል እና ሌሎችም ብዙ ግዜ መስክረውለታል። መጽሀፋቸው ላይ አንድ ምእራፍ ሙሉ ሰጥተው ትንታኔውን ከትበውታል፣ አድናቆታቸውን ችረውታል። መለስ የተደነቀበት የኢኮኖሚክስ እይታ “በድሀ አገር ሙሉ በሙሉ ነጻ ገበያ መፍቀድ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል”፣ “ሉአላዊነታቸውን ያሳጣቸዋል”፣ “በውጭ ባለሀብቶችና ኢንቨስተሮች ቁጥጥር ስር ይወድቃሉ” በሚለው አቋሙ ነው። በኢትዮጵያ ይህን ከምፈቅድ፣ እንደኤሊ ቀስ እያልን ብናዘግም እመርጣለሁ። የሚል ጽኑ አቋም ነበረው። በተለይ ጆሴፍ ስትግልዝ ከባንክና ከመሬት ሊበራላይዜሽን ጋር በተያያዘ በአንዲት ሌሊት ብዙና ጠንካራ የመከራከሪያ ጭብጦችን ማንሳቱ በአግራሞት ያወሳል። በተለይ ከኢስት ኤሽያ ክራይስስ ብዙ ምሳሌዎችን በመጥቀስ፣ ካገሩ ሁኔታ ጋር በማያያዝ አስደማሚ ክርክሮችን ማንሳቱን በአድናቆት መጽሀፉ ላይ ከትቦታል።

ዛሬ ሴንሲብል የሆኑ የአሜሪካ ምሁራን ጆሴፍ ስቲግልዝን ጨምሮ የነጭ ካፒታሊዝም ተቃዋሚዎች ናቸው። ዘ ኢኮኖሚስት በተደጋጋሚ የሚጽፋቸውን አርቲክሎች ላነበበ፣ የስካንዲኔቭያን ዓይነት ኢኮኖሚክ ሞዴል ተግባራዊ ለማድረግ የከጀሉ ይመስላል። በተደጋጋሚ በሚያስተዋውቁት አንድ የሽፋን ገጻቸው “ሶሻሊዝም የነገ ርእዮተ ዓለም” የሚል ምጸት ይዘው ቀርበዋል። የአየር ለውጥ የሚያሳስባቸው ኢኮኖሚስቶችና ፖለቲካል ሳይንቲስቶች፣ እንደዚሁም የአካባቢ ጥበቃ አድቮኬሲ ቡድኖችና ፈላስፋዎች እንደነ Naomi Klein ፣ Noam Chomsky፣ Slavoj Žižek እና የመሳሰሉት አለምን ለማዳን ከነጭ ካፒታሊስት (ነጻ ገበያ) ስርዓት መውጣት አለብን፣ ሲሉ ላንቃቸው እስኪነቃ ድረስ ያቀነቅናሉ።

በአንጻሩ አብይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጣ ጀምሮ ማንም ሳይመርጠውና ይሁንታውን ሳይሰጠው፣ የኢትዮጵያን ህዝብና አገር ወክሎ የሚወስናቸው ውሳኔዎችና የሚፈጽማቸው ውሎች፣ እስከዛሬ ድረስ መለስና ኢህአዴግ አስከብረዉት የነበረ የኢኮኖሚ ሉአላዊነት የሚያስደፍር ነው። ይህ ድርጊቱ የአገሪቱን ሉአላዊነት በረጋግዶ አሳልፎ ከመስጠት ተለይቶ ሊታይ አይችልም። የአለም ካፒታሊስት ስርዓት አራማጅ ወደ መሀል እየመጣ ባለበት፣ በቅይጥ ኢኮኖሚ ስርዓት(ቅድሚያ ላገር ውስጥ ባለሀብት ቦታና ትኩረት በመስጠት) ኢኮኖሚያቸውን እያሳደጉ ያሉ አገራት በተበራከቱበት፣ አብይ ብቻውን ወደዚህ መንደር የሚያደርገው ግስጋሴ ከእንጭጭ ጭንቅላት የመነጨ ከሰራቸውና እየሰራቸው ካሉ ክፋቶች ሁሉ የከፋ ተግባር ነው።

አዎ ኢህአዴግ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ያስመዘገበው እድገት አለ። ከሚያገኘው ከፍተኛ ድጋፍና ብድር ጋር የማይመጣጠን ዝቅተኛ እድገት ቢሆንም የኢኮኖሚ ዕድገት ነበረ። ኢህአዴግ የሚወገዘው እድገት ባለማስመዝገቡ ሳይሆን፣ ህዝብን የዛ እድገት ተጠቃሚ አለማድረጉና የተመዘገበው እድገት ለጥቂቶች ብቻ የተደፋ ዳቦ በማድረጉ ነበረ። በሌላ አነጋገር በግልጽም ይሁን በድብቅ እየዘረፉ ራሳቸውንና በዙሪያቸው ያሉትን ብቻ እየጠቀሙ ሌላውን አድኽይተው ለመግዛት መሞከራቸው ነበር ትልቁና ዋነኛ ስህተታቸው። ይህን ስህተት አብይ በቀላሉ ማረም ይችል ነበር። ገበያውን በረጋግዶ ለውጭ ኮርፖሬሽኖች ልስጥ ማለት አያስፈልገውም ነበር።

ህዝብን የእድገቱ ተጠቃሚ ለማድረግና የተሻለ እድገት እንዲኖር ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበት አሰራር መዘርጋት ነበር የሚያስፈልገው። በሌላ አነጋገር በነጻ ገበያ ስም ያገር ሀብት ከመቸብቸብ በፊት የህግ የበላይነት ማስከበር መቅደም ነበረበት። ሙስኞችን ለህግ ማቅረብ፣ የህዝብ ንብረት ማስመለስ፣ ነጻ ሚድያ፣ ነጻ የፍትህና የኦዲት ስርዓት መዘርጋት ወዘተ በማስቀደም ህዝብን ተጠቃሚ ማድረግ መቅደም ነበረበት። በሒደት የአገር ውስጥ ባለሀብት አቅም ካካበተ ብኋላ እና ዛሬ ለውጭ ባለሀብት ሊበራላይዝ እየተደረጉ ያሉ የመንግስት ኩባንያዎችን በጨረታ ተወዳድሮ የማሸነፍና የመግዛት አቅም ሲፈጥር ነበር፣ ዛሬ እየተወሰደ ያለው የሪፎርም እርምጃ ሊወሰድ ይገባ የነበረው። በሌላ አነጋገር፣ ለአገር ውስጥ ባለሀብት ቅድሚያ በሚሰጥ ፕሮቴክሽኒስት ፖሊሲ ነው ነጻ ገበያ መለማመድ የሚኖርብን።

ከፈረሱ በፊት ጋሪው ቀድሟልና ወደ ተግባራዊነቱ ከመሸጋገሩ በፊት የሚመለከታቸው አካላት፣ ዩኒላተራሊ እየተወሰነ ባለው በዚህ ሰውዬ አካሔድ ላይ ልጓም ቢጤ ቢያኖሩለት ይመከራል።

ስራ አጥነት፣ አለመረጋጋትና የስደተኞች ከካምፕ መውጣት እንደምታው

የኢትዮጵያ መንግስት ወደ አንድ ሚልዮን የሚጠጉ ስደተኞች ከካምፕ ወጥተው ወደ ስራ እንዲሰማሩ መፍቀዱ በመገናኛ ብዙሀን ተነግሯል። ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ዓለማችን ብዙ አስገራሚ ነገሮችን ስታስተናግድ አይተናል። የትራምፕ ፕሬዚደንት ሆኖ መመረጥ፣ የBrexit ህዝበ ውሳኔ፣ እንዲህውም በአውሮፓና በአሜሪካ የኒዮናዚ አቀንቃኞችና ጽንፈኛ ብሔርተኞች ማንሰራራት፣ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ስደተኞችን ከሚመለከት ፖሊሲና ፖለቲካ ጋር ተያይዞ የመጣ ቀውስ እንደሆነ ይነገራል። የኢትዮጵያ መንግስት የወሰነው ውሳኔ ቀላል የማይባል የፖለቲካ ውሳኔ እንደመሆኑ መጠን ጥቅምና ጉዳቱ ምንድን ነው የሚለውን እንመለከታለን።

1. ጥቅሙ

1.1 ከዲፕሎማሲ አንጻር –

ሀ. ድሀዋ ኢትዮጵያ በግዛቷ ስር ላሉ ስደተኞች የምታደርገው መልካም አያያዝ ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብና መንግስታት አርአያ የሚሆን በጎ መልእክት ያስተላልፋል።
ለ. ለሌሎች አፍሪካውያን ወንድሞቻችን በራችን ክፍት መሆኑን ያበስራል። ጥሩ ተምሳሌት በመሆን፣ በአፍሪካ በተለያዩ አገራት በስደት ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን መልካም አያያዝ እንዲደረግላቸው ጥሩ መልእክት ያስተላልፋል።

1.2 አገር ውስጥ –

ሀ. ጎሰኝነትን ቶሎ ለማርከስ ከኢትዮጵያዊነት በላይ ልቆ ማቀንቀን ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ፓን አፍሪካኒዝም ቀዳሚው አማራጭ ነው። ፓን አፍሪካኒዝም በተግባር እውን ሊሆን የሚችለው ደግሞ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ከአህጉራችን ለሚመጡ ሰዎች በራችንንና ልባችንን ክፍት ማድረግ ስንችል ነው። አብረውን ሲሰሩ፣ አብረናቸው ስንኖር፣ በጓደኝነትና በትዳር አጋርነት መተሳሰር ስንጀምር በሂደት ወደ ታች (ወደ ጎሳ) ማየቱን እየተውን ወደ ከፍታው እንድንመለከት ይረዳን ይሆናል።
ለ. ስደተኞቹ ስራ ፈትተው ካምፕ ውስጥ ተጎልተው የመጽዋቾችን እጅ ከሚጠባበቁ፣ ወደ ስራ ተሰማርተው፣ ኢኮኖሚያችን ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ በማበርከት፣ ለመንግስት ግብር በመክፈል፣ ሸማቹን ማህበረሰባችንን ተቀላቅለው ምርታችንን በመግዛት እንዲህውም ለአገራቸው በማስተዋወቅ (የኤክስፖርት አቅማችንን የማጎልበት ፋይዳ አለው!) ዘርፈ ብዙ ጥቅም ሊያስገኙልን ይችላሉ። በተጨማሪም ከካምፕ የወጣ ሰው ስራ አያማርጥምና ካገኘም ስራ ላይ አይለግምምና፣ ልንማርበት የምንችል የስራ ባህል በማካፈል ረገድ ሊጠቅሙን ይችላሉ።

2. ጉዳቱ (ስራው ከየት ይመጣል?)

ኢትዮጵያ ያልተረጋጋች፣ በሁሉም አቅጣጫ ግጭት የበዛባት፣ መጨረሻው ሊተነበይ በማይችል የለውጥ ማእበል እየተናጠች ያለች አገር ናት።
የለውጥ ማእበሉን የቀሰቀሰው፣ ስራ አጥነትና የኑሮ ውድነት ያሰቃየው ወጣት ነው። ይኽ ወጣት የስርዓት ለውጥ አመጣ እንጂ፣ ኑሮው ላይ ገና ለውጥ አላየም። መንግስት የተጠመደው መሰረታዊ የሚባሉ መዋቅራዊ ሪፎርሞችን በማካሔድ ነው። ስራ የሚፈጥሩ ፕሮግራሞችንና ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ስራ አጡን ወጣት የማረጋጋት ስራ ገና አልጀመረም። ባልተረጋጋ አገር ውስጥ የኢኮኖሚ ድቀት ሲታከልበት፣ ወጣቱ ወደ ወንጀል የመሰማራቱ እድል ይጨምራል።
መንግስት ሙሉ ትኩረቱን ሌላ ቦታ ላይ ባደረገበት በአሁኑ ወቅት፣ በመዋቅራዊ ለውጡ ምክንያት ጥቅሙ የተነካበት ኪራይ ሰብሳቢ ኤሊት ለውጡን ለማደናቀፍ ተግቶ እየሰራ እንዳለ ባደባባይ የሚታወቅ ሀቅ ነው። ይህ ሴራም እየተከናወነ ያለው፣ ገንዘባቸውን በመርጨት ስራ አጡን ወጣት ለጥፋትና ለነውጥ ማሰማራት በመቻላቸው ነው። ስለ ሰላም በሚዘመርበት ወቅት ታጣቂና ተደራጅቶ የሚዘርፍ ማፊያ እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አልመጣም። ቀድሞውኑ መንግስት ወጣቱን ወደ ስራ ለማሰማራት ቅድሚያ ሰጥቶ መንቀሳቀስ ሲገባው ቸልተኛ መሆኑ ሳያንስ አሁን ደግሞ አንድ ሚልዮን የሚጠጋ ስራ የሚቀራመት “ተፎካካሪ” ስደተኛ የlabor marketኡን እንዲቀላቀል መወሰኑ አደጋ ያለው አካሔድ ይመስለኛል። ይኽ ያለውን ያለመረጋጋት ሁኔታ ከማባባስ አልፎ በስደተኞቹ ላይ ጥላቻ ለማሳደርና ለግጭት እንዳይጋብዝ ያሰፈራል። ከዚህ በተጨማሪ ከጸጥታና ደህንነት ጋር የተያያዙ ችግሮች ሊፈጠሩ ይችላሉ። እንዴት ለሚለው ጥያቄ በአጭሩ እንመልከት።
የኢትዮጵያ ህዝብ በየዓመቱ በ2.5% ያድጋል። በዓመት ከሁለት ሚልዮን በላይ ማለት ነው። ከአመት በፊት በነበርንበት ሁኔታ ለመቀጠል፣ መንግስት በዚህ ዓመት ቢያንስ ለ2 ሚልዮን ዜጎች ስራ መፍጠር አለበት። 1 ሚልዮን ስደተኛ ከጨመርንበት ደግሞ፣ ቢያንስ ለ3 ሚልዮን ሰው ስራ መፍጠር አለበት። ይህን ማድረግ ካልቻለ ዘርፈ ብዙ ቀውስ ይፈጠራል። ስደተኛው ራሱ ከካምፕ ወጥቶ ስራ ካጣ ወንጀል ውስጥ ሊዘፈቅ ይችላል። ኢህአዴግን ለውድቀት ከዳረጉት ምክንያቶች አንዱ ምናልባትም ግንባር ቀደሙ፣ ከህዝብ ቁጥራችን ጋር መመጣጠን የሚችል ስራ በየዓመቱ መፍጠር ባለመቻሉ ነው። የዘንድሮ ከአምናውና ካካቻምናው እየባሰ ሲሔድ፣ ሲጠራቀም፣ ሞልቶ የፈሰሰ ዕለት ነው፣ ጎርፍ ሆኖ ጠራርጎ የወሰደው። ዛሬም የስራ አጡንና የህዝብ እድገቱን የሚመጥን ስራ መፍጠርና አገሪቱን ማረጋጋት ባልቻለበት ሁኔታ፣ ይህን ውሳኔ መወሰኑ፣ ለ22 ተጫዋችና ለ3 ዳኛ ብቻ በሚፈቀደ ሜዳ ላይ ተመልካቹንም ፈትቶ እንደመልቀቅ ይቆጠራል።