በአዲስ አበባና በሌሎች ከተሞች የሚታይ ችግር ለመፍታት የቀረበ አማራጭ ሀሳብ

በሰለሞን ነጋሽ

Global warming ዓለምን የሚያሳስብ ትልቅ አጀንዳ ሆኖ ብቅ ካለ ወዲህ ወሳኝ የሆነ አለም አቀፍ ስምምነት የተደረገው የKyoto Protocol ተብሎ የሚታወቀው ስምምነት ይመስለኛል። ከዛ ስምምነት ብኋላ የረባ ስምምነት ተደርጎ ነበር ከተባለ በፕሬዝደንት ኦባማ አማካኝነት አሜሪካ ለመጀመሪያ ግዜ የተቀበለችውና የተፈራረመችበት የፓሪሱ ስምምነት ነበር። ኋላ ላይ እንደምታውቁት ፕሬዚደንት ትራምፕ ስምምነቱን ሰርዞታል። ከኪዮቶ ብኋላ ስራ ተሰርቷል ከተባለ፣ የስምምነቱ አባል አገራት ቁጥር መጨመርና በፓሪስ ስምምነት የተደረሰው Global average temperature ከ2ና ከ1.5 ዲግሪ ሴንትግሬድ በላይ መጨመር የለበትም የሚለው ነው።

የኪዮቶ ፕሮቶኮል ለየት ከሚያደርጉት ብዙ ርእሰ ጉዳዮች መካከል አንዱ ሁሉም አገራት መልቀቅ የሚችሉት የካርቦንዳይኦክሳይድን መጠን በኮታ ማስቀመጡና ከተቀመጠው ኮታ በላይ እንዳይሔዱ ለመገደብ የሚረዱ 3 አማራጭ policy instruments ማስቀመጡ ናቸው። እነዚህም Emission Trading, Joint Implementation Mechanism እና Clean Development Mechanism በመባል ይታወቃሉ።

  1. Emission Trading የሚባለው አሰራር፣ አገራት ከኮታቸው በላይ አየሩን የሚበክሉ ከሆነና መቀነስ የማይችሉ ከሆነ፣ ኮታቸውን መጠቀም ከማይችሉ ድሀ አገራት መግዛት የሚችሉበትን አሰራር ያስቀምጣል። በመሰረታዊ የኢኮኖሚክስ አቅርቦትና ፍጆታ ጽንሰ ሀሳብ ላይ የተመሰረተ አሰራር ነው። ሀብታም አገራትን ከመጠን በላይ አየሩን እንዲበክሉ የሚያበረታታ አሰራር ነው ተብሎ በስፋት ይተቻል። የአየር ብክለትና ሙቀት መጨመር በዋጋ ሊተመን የማይችል መዘዝ አለው። ያንን በምን መልኩ ግምት ውስጥ አስገብቶ ኮታ መሸጥና መግዛት ይቻላል? ድሀ አገራት ቶሎ ተጠቃሚ ለመሆን እንደማንኛውም ሸቀጥ በዝቅተኛ ዋጋ ለመሸጥ በገበያ ላይ ይፎካከራሉ እንጂ ትክክለኛ ዋጋው የሚገምትናና ኮስቱን ኢንተርናላይዝ የሚያደርግ የገበያ ስርዓት አይከተሉም። እንደሚታወቀው ሀብታምና ከኮታቸው በላይ ሊጠቀሙ የሚችሉ አገራት ከድሆቹና ኮታቸውን መሸጥ ከሚፈልጉ አገራት በቁጥር ያንሳሉ። አቅራቢው በዝቶ ገዢው ሲያንስ የመሸጫ ዋጋ በጣም ይቀንሳል። በመሆኑም የሻጮቹ ፉክክር ዋጋውን ለመቀነስ ወደ ታች ነው(ፈረንጆቹ Race to the bottom ይሉታል)። ይህ ፉክክር ሀብታም አገራት ይበልጥ አየር እንዲበክሉ ያበረታታል። የአየር ብክለትና ሙቀት መጨመር ዋንኛ ተጠቂውና የገፈቱ ቀማሽ ድሃው ነውና ይህ ፉክክር የማታ ማታ ድሃውን ይበልጥ ተጎጂ ያደርገዋል።
  2. Joint Implementation Mechanism ( JIM) – የሚባለው አሰራር በሀብታም አገራት ብቻ የተወሰነ ነው። ዋናው ጭብጥ Comparative Advantage ከሚባለው የDavid Ricardo ጽንሰ ሀሳብ የተቀዳ ነው። በRicardo ጽንሰ ሀሳብ አንድ አገር ከሌላ አገር በንጽጽር የተሻለ አድቫንቴጅ አለው የሚባለው ተመሳሳይ ምርት ለማምረት የሚያወጣው ወጪ የሚቀንስ ከሆነ ነው። የJIM Ricardo ጽንሰ ሀሳብ ጽንሰሀሳብ የሚለየው ወጪው በገንዘብ ብቻ ሳይሆን በካርቦንዳይኦክሳይድ ልቀት መጠንም የሚለካ መሆኑ ነው። ለምሳሌ መኪናና የጦር መሳሪያ የሚያመርቱ አገራት፣ አንደኛው የጦር መሳሪያ ሲያመርት ከሌላኛው በተሻለ ዝቅተኛ የአየር ብክለት የሚያስከትል ከሆነና ሌላኛው መኪና ሲያመርት ዝቅተኛ ብክለት ካለው ሁለቱ አገራት በነዚህ ዘርፎች ተጣምረው በመስራት እያንዳንዳቸው ስፔሻላይዝ ባደረጉበት(ብክለት የሚቀንሰውን)ዘርፍ በማምረት ኤክስፖርት ይደራረጋሉ። ዋነኛ ስምምነታቸው ቅድሚያ አብሮት ለሚሰራ አገር ኤክስፖርት ሳያደርግ ለሌላ መሸጥ አይችልም። አብረው በመስራት የሚጠቀሙ ከንግድ ልውውጥ ብቻ ሳይሆን፣ በጥምር አሰራራቸው ለቀነሱት ብክለትም ተመጣጣኝ ገንዘብ ይከፈላቸዋል። የሚከፈለው ገንዘብ ሌሎችም አሰራሩን እንዲከተሉ ያበረታታል። JIM ከመጀመሪያው አማራጭ የተሻለ ቢሆንም፣ ድሀ አገራትን ከነአካቴው ያገለለ አሰራር ነው። ድሀ አገራት ጥሬ እቃ እንጂ ያለቀ ምርት የሚያቀርቡበት እምብዛም እድል የለም። ካላቸውም ኋላቀር በሆኑ ፋብሪካዎች የሚመረቱ እቃዎች ስለሚሆን ብክለታቸው የከፋ እንጂ የቀነሰ ስላማይሆን የዚህ አሰራር ተጠቃሚ የሚሆኑበት እድል የለም። ስለሆነም ሶስተኛው አማራጭ እነሱን ታሳቢ አድርጎ የቀረበ ነው።
  3. Clean Development Mechanism (CDM) – ይህ አሰራር ሁለት ግቦችን ታሳቢ አድርጎ የተቀረጸ ነው። አንደኛው ብክለት መቀነስ(Emission Reduction)ሲሆን ሁለተኛው ድሆችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ (contribution to sustainable development) ነው። የዚህ አሰራር ብዙ አይነት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክቶች አሉ። እንደ ምሳሌ የሀይል ማመንጫ ግድብ መስራት፣ ደን ማልማት፣ ቆሻሻ ማስወገድ፣ ባዮጋዝ ማምረት፣ከጸሃይና ከንፋስ ሀይል ማመንጨት፣ ወዘተ መጥቀስ ይቻላል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በድሀ አገራት መሰራት ያለባቸው ናቸው። ብክለትን ከመቀነስ ጎን ለጎን፣ ለድሀው የስራ እድል በመፍጠር፣ አማራጭ የኤሌትሪክ ሀይል በማቅረብ፣ አካባቢን በማጽዳትና የጤና ሁኔታን በማሻሻል፣ ምርትን በማሳደግ፣ ወዘተ ተጠቃሚ ማድረግ አለባቸው። በCDM አሰራር መሰረት ሁለቱን ግብ የሚያሟሉ ፕሮጀክቶች፣ ለቀነሱት ብክለት (የተቀነሰው የብክለት መጠን የሚጠቅስ) Certified Emission Reduction (CER) የሚባል ሰርትፍኬት ይሰጣቸዋል። ሰርትፍኬቱን በዓለም ገበያ ለትላልቅ ኩባንያዎችና መንግስታት መሸጥ ይችላሉ። CER የሚሸጥና የሚገዛበት ስቶክ ማርኬትም አለ። ገዢዎቹ ሰርትፍኬቱ ላይ የተጠቀሰውን መጠን ያህል ብክለት እንደቀነሱ ይታሰብላቸዋል። ከኮታቸው ካለፉ ወይም የሚያልፉ ከሆነ ይህ ያካክስላቸዋል። አንዳንዶች ከኮታቸው ሳይደርሱም ይገዛሉ። ለጥሩ አርአያነት፣ የምርት ስታንዳርዳቸውን ከፍ ለማድረግ፣ ብሎም ደንበኞቻቸውን ለማስደሰት። ኢኮ-ፍሬንድሊ ምርቶች በገበያ ላይ ተፈላጊ ለምን እንደሚሆኑ መዘርዘር አያስፈልገኝም። አንድ የማርኬቲንግ ስትራቴጂ መሆኑን ብቻ ላስምርበት።

በCDM አሰራር ማንም ሰው እነዚህን ፕሮጀክቶች በግሉም በቡድንም በኩባንያም ይሁን በአገር ደረጃ ማንቀሳቀስ ይችላል። የግድ ፋብሪካ ያለውና ብክለቱን መቀነስ የሚፈልግ ድርጅት ወይም መንግስት ብቻ መሆንን አይጠይቅም። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ብዙ ጥቅም ማግኘት ስትችል በስንፍናዋ ምክንያት ተጠቃሚ ሳትሆን ቀርታለች። ለምሳሌ ደን የሚያለሙ አርሶ አደሮች በማህበር ተደራጅተው ባለሙት መጠን ያህል ድጎማ የሚያገኙበትና ሰርትፍኬት የሚያገኙበት እድል አለ። ያንን ሰርትፍኬት ሸጠው ገንዘብ የሚያተርፉበት እድል አለ። ትርፉ ሁለት ግዜ ነው። አካባቢህን ታለማለህ፣ የልማቱ ተጠቃሚ ትሆናለህ፣ ስላለማህ ደግሞ ገንዘብ ታገኛለህ።

ይህ ፕሮጀክት ገጠርን ብቻ ታሳቢ ያደረገ አይደለም። ከተሞችም በስፋት ተጠቃሚ ናቸው። ለምሳሌ አዲስ አበባንና ሌሎች ከተሞችን የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚ በማድረግ ብቻ ከተሞቹን እስከወዲያኛው መቀየር ይቻላል!የዚህ ጽሁፍ መነሻ ምክንያትና ዋና ዓለማ የአዲስ አበባን ችግር ለመፍታት ሙያዊ ጥቆማ ለመስጠት ስለሆነ፣ ከዚህ ፕሮጀክት በምን መልኩ አዲስ አበባ ተጠቃሚ መሆን እንደምትችል ከብዙ እምቅ ፕሮጀክቶች ከአንዱ ማለትም ቆሻሻ ከማስወገድ ብቻ ልታገኝ የምትችለውን ጥቅም አንድ በአንድ እዘረዝራለሁ።

አዲስ አበባን ከቆሻሻ የጸዳች በማድረግ ሊገኙ የሚችሉ ዋና ዋና ጥቅሞች :-

  1. ከጤና አኳያ – የሰው ህይወት ከሞት ይታደጋል። ተያያዥ የጤና መታወኮች የሚያስከትሉት ወጪ(በቢልዮን ባይገመት በሚልዮኖች የሚገመት)መቀነስ ይቻላል። ያ ወጪ ለሌላ ልማት ለምሳሌ ለትምህርት ሊውል ይችላል። ጤና ሲሻሻል ደግሞ የስራ ባህሪና ምርት ላይ የሚያሳየው እምርታ ይኖራል።
  2. የጥቅም ግጭት ከመፍታት አኳያ – በዙሪያዋ ካሉ አርሶ አደሮች ጋር በቆሻሻ ፍሰት ምክንያት በየጊዜው ፍጥጫ የምትገባበትን ሁኔታ ያስቀራል ወይም ይቀንሳል። እነዚህ ፍጥጫዎች እየተለጠጡ ትልቅ አገራዊና ፖለቲካዊ አጀንዳ ሆነው የከተማዋንና የአገሪቱን ህልውና የሚፈታተኑበት ሁኔታ ያከትማል።
  3. ቆሻሻን ለጥቅም ከማዋል አኳያ – በከተማዋ ዙሪያ በአራቱም አቅጣጫ ባዮጋዝ የሚያመርቱ፣ ሪሳይክል የሚያደርጉ፣ ወዘተ ፋብሪካዎችን በመትከል (የግል ባለሀብቱን በማሳተፍና የብድር አቅርቦታን በማሻሻል)፣ ቆሻሻውን መልሶ ጥቅም ላይ ማዋልና ከተማዋና በዙሪያዋ ያሉ አርሶ አደሮች የሪሳይክልድ ምርቱ ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሁኔታ መፍጠር ይቻላል። ቁልፉ ስራ ያለው ደግሞ እዚህ ላይ ነው። በቆሻሻ ምክንያት ከተሜውና ገጠሩ መታመም፣ ገበሬው የእርሻ መሬቱ መባከን፣ ምርቱ መበላሸት ሳይኖርበት፣ የሀይል ምንጭና የሌላ እቃ ማምረቻ ግብአት በማድረግ የሚገኘው ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና አካባቢያዊ ጠቀሜታ መገመት ይቻላል።
  4. የተቀናጀ አሰራር ከመፍጠር አኳያ – የከተማዋ የውሃና ፍሳሽ አገልግሎት አሰራር በማሻሻል፣ የሰው ሀይልና በጀት በመጨመር፣ ከባለሀብቶች ጋር በማቀናጀት ቆሻሻ የሚከማችበት፣ የሚወገድበትና ሪሳይክል የሚደረግበትን የዘመነና የተሳሰረ አሰራር በዝቅተኛ ወጪ መስራት ይቻላል። ግብር ከፋዩ የከተማዋ ኗሪ ለዚህ የሚሆን ቀርቶ ለሌላ አገልግሎት የሚተርፍ ከዛም በላይ ይከፍላል። እየከፈለም ነው። ለግዜው የተራቆተ ካዝና ከሆነም የተረከብነው፣ በብድር ፕሮጀክቱን ማስኬድ ይቻላል። ኢኮኖሚክ ሪተርኑ የት የሌለ ነው።
  5. የስራ እድል ከመፍጠር አኳያ – ይህ እርምጃ ለከተማዋ ድሃና በዙሪያዋ ላሉ አርሶ አደሮች ከፍተኛ የስራ እድል ይፈጥራል። ቢያንስ ለ5ሺ የተማረና ያልተማረ የሰው ሀይል የስራ እድል ይፈጥራል። የስራ እድሉ ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎች ቤተሰብ ማስተዳደር፣ መማር፣ ወዘተ የሚችሉበትን እድል ይፈጥራላቸዋል። በስራ አጥነት ምክንያት ወንጀልና ነውጥ ውስጥ ሊሳተፍ ይችል የነበረውን ዜጋ ምርታማ ዜጋ ለማድረግ ይረዳል።
  6. በCER ከሚያስገኘው ገቢ አኳያ – በዚህ ፕሮጀክት አማካኝነት የተቀነሰ የአየር ብክለት ተገምቶ፣ ለአካባቢው ድሀ ያስገኘውን ፋይዳ ታሳቢ ተደርጎ፣ በCDM አሰራር መሰረት ለዓለም ገበያ የሚቀርብና ወደ ገንዘብ ሊቀየር የሚችል ሰርትፊኬት ማግኘት ይቻላል። ከዚህ ብቻ የሚገኘው ገቢ፣ የፕሮጀክቱን ወጪ ቢያንስ ግማሹን የመሸፈን አቅም አለው። በተጨማሪም በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ የተሰማሩ ግብረሰናይ ድርጅቶች፣ የሀብታም አገራት መንግስታትና ትላልቅ ኩባንያዎች የገንዘብ፣ የሰው ሀይልና የቁስ እርዳታ የማድረግ እድላቸው ከፍተኛ ነው።
  7. በዲፕሎማሲና በቱሪዝም ዘርፍ ከሚያስገኘው ፋይዳ አኳያ – በመጨረሻም አዲስ አበባ በቆሻሻ ምክንያት በዙሪያዋ ካሉ አርሶ አደሮች ጋር እየተፋጠጠች፣ ለራእይ አልባ ፖለቲከኞች ሲሳይ ሆና የራሷንና የአገራችንን ህልውና ከመፈታተን ተላቅቃ፣ ከተማዋ ለአካባቢ ጥበቃ በምታደርገው እንቅስቃሴ ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ጥሩ ምሳሌ በመሆን፣ በአለም አደባባይ የምትደነቅበትና ከአፍሪካ መዲናነት አልፋ የአለም መዲና መሆን የምትችልበትን አጋጣሚ መፍጠር ትችላለች። ይህ በራሱ ትልቅ ስኬት ሆኖ፣ በቱሪዝም ዘርፍ ልታገኝ የምትችለውን የገቢ አቅም ከማሳደግ አኳያም እድሏ ሰፊ ነው።

በደንብ ከታሰበበትና ከተሰራበት ይህ ከ5 እስከ 10 ዓመት ባለው ግዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ እውን መሆን ይቻላል።

እንግዲህ ከላይ የተመለከትነው በዙሪያው ብዙዎችን ማሳተፍ ከሚችል ከአንድ ትልቅ ከተማ ማእከሉን ያደረገ ፕሮጀክት በCDM በመታገዝ ሊገኝ የሚችል ጥቅም ብቻ ነው። በሌሎች ከተሞች ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ማከናወንና የCDM ተጠቃሚ መሆን ይቻላል። በአዲስ አበባም ሌሎች ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተጠቃሚ መሆን ይቻላል። በየገጠሩ ደግሞ ገበሬውን አስተባብሮ በሚያለሙትና በሚጠብቁት ደን ልክ ተጠቃሚ ማድረግ ይቻላል። የተፈጥሮ ጫካን በመጠበቅና በማስጠበቅ ብቻ የREDD+ ተጠቃሚ በመሆን በየአመቱ ዶላር መዛቅ ይቻላል። የሜቴክ ኢንጅነሮች ደን ለመመንጠር በቢልዮን የሚቆጠር ብር ይበጅቱ ነበረ። ያ ደን ባለበት ለአካባቢው ከሚሰጠው ጥቅም ባሻገር የገንዘብ ምንጭ መሆን እንደሚችል ማወቁ አይከፋም። ምናልባት ደኑ ከተመነጠረ ብኋላ ሊቋቋሙ ከሚታሰቡት ፋብሪካዎች በላይ የተሻለ ገቢ ሊኖረው ይችላል።

ወጣቶች፣ ምሁራንና የፖሊሲ አማካሪዎች ይህን ሊንክ (http://cdm.unfccc.int/Projects/projsearch.html)ተከትላችሁ ምን ዓይነት ፕሮጀክቶች በCDM እንደመተዘገቡና የEmission Reduction ሰርትፊኬት ለማግኘት እየተጠባበቁ እንደሆነ እንድትመለከቱ ልጋብዛችሁ። እኛ ልንሰራውና ተጠቃሚ ልንሆን የማንችልበት ፕሮጀክት እንደሌለ ማየት ትችላላችሁ። የሚያሳዝነው ከ2 አስርት ዓመታት በላይ ባስቆጠረው የCDM ፕሮጀክት በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ፕሮጀክቶች ተመዝግበዋል። እየተመዘገቡም ነው። ከኢትዮጵያ ተጠቃሚ ለመሆን የተመዘገቡት 30 አይሞሉም። ያውም አብዛኛዎቹ በውጭ ግብረሰናይ ድርጅቶች የሚመሩ ፕሮጀክቶች ናቸው።

ህይወታችንን ሊቀይሩ የሚችሉ ብዙ አማራጮችን ዘመኑ መዳፋችን ስር አቅርቦልናል። ለችግሮቻችን ዘላቂ መፍትሔ ሊያመጡ የሚችሉ አማራጮች ሁሉ አሉ። እነዚህን እየቃኘን ተጠቃሚ በመሆን የራሳችንና የዜጎችን ህይወት ለማቃናት እንሞክር።

ሰላም!

የጸሀፊው መብት በህግ የተጠበቀ ነው!

2 replies
  1. Desalegn
    Desalegn says:

    ወንድም ሰሎሞን ታላቅ ምስጋና ላቀረብከው ድንቅ ሀሳብና ትንተና። አረንጓዴ ኢኮኖሚ ፣የማህበረሰብ ተሳትፎና ባለቤትነትና ውጤታማ ያልተማከለ አሰራር ለቀጣይ የአዲስ አበባ እድገት አይነተኛ ሚና ይጫዎታሉ። ።ከንቲባ ታከለ “transforming the last block” የሚል ከላይ የተጠቀሱትን ያካተተ የተቀናጀ ስትራቴጂ እንዲያስጀምሩ እጠይቃለሁ።

    Reply

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *