ከአርቲስት ሀጫሉ ግድያ በስተጀርባ ….

… በሆነው ነገር ከማዘን በላይ ተበሳጭቼ፣ ምንም ላለማለት ወስኜ ነበር። ነገር ግን ዝምታዬም ያስወቅሰኝ ጀምሯል። ታድያ … የሚሰማኝን ልጻፍና …

በቅድሚያ አንድ ነገር ልበል። በዚህ እድሜው በሰው እጅ ቀርቶ በበሽታም መሞት የማይገባው ወጣት ነበር አርቲስት ሀጫሉ። በፖለቲካ አመለካከቱ ባንግባባም፣ የሚያወራው ባይጥመኝም፣ ምናምን የሚል ቅራቅንቦ አልደርትም። ምንም ይሁን ምን ግድያውን ፍጹም አወግዛለሁ!! ገዳዮቹና አስገዳዮቹ (ህግ አስከባሪ የለም እንጂ) ለህግ ቀርበው የእጃቸውን ማግኘት እንዳለባቸውም አምናለሁ። በዚህ አጋጣሚ በአርቲስት ሀጫሉ ሞት፣ በሀዘን ልባቸው ለተሰበረ በሙሉ (አስመሳዮች የአዞ እንባ የሚያነቡትን ሳይጨምር) መጽናናትን ከልብ እመኛለሁ። እንዲህውም ከግድያው ብኋላ በተፈጠረ ቀውስ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች ሀዘኔ ጥልቅ ነው። ለቤተሰቦቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን እመኛለሁ።

እንግዲህ ከሀጫሉ ግድያ በስተጀርባ ማን ሊሆን እንደሚችል ብዙ መላምቶችን ከተለያዩ አቅጣጫዎች እየሰማን ነው። ሞቱን ተከትሎም ሁሉም በየአቅጣጫው ለፖለቲካ ፍጆታው እየተጠቀመበት ነው። ለፖለቲካ ፍጆታ እንደሚውልና አመጽ እንደሚያቀጣጥል የሚጠበቅ ነበር። ለጊዜው መንግስት ነኝ የሚለው የአብይ ቡድን፣ ገዳዮቹ እነማን እንሆኑ እያጣራን ነው ባለበት ቅጽበት፣ ህወሓት ነው፣ ግብጽ ነው፣ የግብጽ ተላላኪዎች ናቸው፣ የሚሉ የተለያዩ ግራ የገባቸው ውንጀላዎችን ሰንዝሯል። ህግ ይዞታል ከተባለ፣ ተጣርቶ ሳያልቅ እንዲህ አይነት ውንጀላ፣ መነሻውና ጥቅሙ ምንድን ነው? የዛሬ ሁለት አመት፣ የምርመራ ውጤቱ ከመታወቁ በፊት ህወሓት ነው ከዚህ በስተጀርባ ያለው ብሎ የከሰሰው መሪ፣ ውጤቱ ሲታወቅ እስከዚች ደቂቃ ድረስ ይፋ እንዳላደረገ ይታወቃል። የዛሬ አመት ለተፈጠረው ግድያ በተመሳሳይ መልኩ ከምርመራው በፊት ጣቱን ሌሎች ላይ ቢቀስርም፣ የሆነው ግን ሌላ ሆኖ የተገኘው። ውጤቱም እስከአሁኗ ደቂቃ ድረስ ለህዝብ አልተነገረም። በመካከላቸው ለተፈጠረው አለመግባባት ተጨማሪ ቤንዚን ሆነ አገለገለ ይበልጥ መካረር ውስጥ ከተታቸው እንጂ የፈየደው ነገር አልነበረም። ዛሬም ምርመራ ከመካሔዱ በፊት ውንጀላው አንድ ቡድን ላይ (ህወሓት ላይ) አድርጎ እያደነ የሚያስረው ደግሞ ሌላ ቡድንን (የእነ ጀዋር) ነው። ህወሓት/ግብጽ ከሆነ ሀጫሉን የገደለው ኦሮሚያ ላይ የብልጽግና ውጋት የሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚመሩ የፖለቲካ መሪዎችና ጋዜጠኞች ለምን እየታድኑ ታሰሩ?

ተጣርቶ እስኪታወቅ ድረስ መላምት መደረት የሚቻል ከሆነ፣ ከአጫሉ ግድያ በስተጀርባ ህወሓት፣ የኦሮሞ ብሔርተኞቹ፣ የግብጽ ተላላኪዎች ሊኖሩ ከቻሉ፣ አብይ ራሱ ሊኖር የማይችልበት ምክንያት ምንድን ነው? እስኪ በዝርዝር እንመልከተው። በአባይ ግድብ ዙሪያ በተደጋጋሚ እንዳየነው እርሱ የተካፈለበት ድርድር፣ የአገርን ሉአላዊነት አሳልፎ የሚሰጥ ነበር። በመጀመሪያ አሜሪካና የዓለም ባንክ አደራዳሪ እንዲሆኑ የተስማማው አብይ ነው። ሲቀጥል በሁለት ሳምንት ውስጥ ስምምነት ላይ መደረስ አለበት፣ ስምምነት ላይ ከመድረሳችን በፊት ግድቡን መሙላት አንጀምር ብሎ ግብጽን ያስፈነጠዘ ስምምነት የፈጸመው አብይ ነው። አጫሉ በተገደለበት እለት ደግሞ፣ ግድቡን የመሙላት ሂደት የመብት ጉዳይ ሳይሆን፣ የጦርነት ጉዳይ ይመስል፣ የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳ እንዲሆን ያደረገው አብይ ነው። እዛ ደግሞ ምን አይነት ስምምነት አድርጎ እንደመጣ አናውቅም። ምናልባትም ከዛ አጀንዳ ለማስቅየስ የተደረገ፣ ብሎም አገርን በማበጣበጥ፣ ግድቡን የመሙላት ሂደት ለማዘግየት የተቀነባበረ ሴራም ሊሆን ይችላል። በነገራችን ላይ በነዚህ ጉዳዮች ጀዋር ሲያራምድ የነበረው አቋም፣ እንደ አንድ ፖለቲከኛ ሳይሆን እንደ አንድ አገር መሪ ነበር። እንዲያውም መጨረሻ ላይ፣ በዲፕሎማሲው ረገድ ደህና ድል እያገኘን የነበረውን ሁኔታ የቀለበሰው፣ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ስራውን እንዳይሰራ ስለተደረገ ነው፣ የሚል ስሞታ አሰምቷል። አብይን በአገር ጉዳይ የማያምነው መሆኑ፣ ልክ ብዙዎቻችን የታዘብነውን አይነት ክህደቶችን የታዘበ መሆኑን የሚያሳይ ፍንጭ ጽፎ ነበር። በእርግጥ ግብጽን አልጎዳም ብሎ በማያውቀው ቋንቋ ደጋግሞ የማለውና የተገዘተው ማን እንደሆነ ሁሉም ያውቃል።

ይህን ግድያ አብይ ከግብጽ ጋር ያለውን ጉዳይ ለማለዘብ ብቻ ሳይሆን፣ ተቀናቃኞቹን ለመስበርም እየተጠቀመበት ያለ ይመስለኛል። ከላይ እንዳልኩት ኦሮሚያ ላይ፣ ሰማይ ምድሩ ቢገለበጥ፣ በነጻ ምርጫ ሊያሸንፋቸው የማይችሉ ተቀናቃኞቹ ለማሰር ተጠቀሞበታል። የኦሮሞ ተቀናቃኞቹን ከሰበረ ብኋላ በሙሉ ጉልበት ፊቱን ወደ ህወሓት ማዞር ነው ስሌቱ። ያው የጅል ስሌት ነው። ፊቱን ወደ ሰሜን ከማዞሩ በፊት፣ ኦሮሚያ ላይ በማሰው ጉድጓድ ራሱን ያገኘዋል። የት ድረስ እንደሚያዛልቀው እንኳን በደንብ ያሰላው አይመስልም። ለእርሱ ታማኝ የሆኑ አንድ ሁለት ቀበሌ ማተራመስ የሚችሉ ልዩ ሃይሎች ቢኖሩትም፣ የሚያስመካና ልትተማመንበት የምትችል ጉልበት ያላቸው አይደሉም። ሁሉም የተነሳባቸው እለት ድራሻቸው አይገኝም።
ከዚህ ሁሉ ግን፣ ከተቀናቃኞቹ ጋር ያለውን ችግር በድርድርና በውይይት ቀድሞ ፈትቶ ወይም ለመፍታት ሞክሮ ቢሆን ኖሮ ይህ ሁኔታ ሊፈጠር ይችል ነበር? አይመስለኝም። ምክንያቱም እርሱም ሆኑ ሌሎቹ ችግራቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ፣ በሰለጠነ መንገድ ከፈቱ የዚህ አይነት ሴራ ውስጥ መግባት አያስፈልጋቸውም ነበር። ለዚህ እነ ጀዋርም፣ ህወሓትም ሌሎችም ዝግጁ መሆናቸውን በተደጋጋሚ በግልጽ ሲናገሩ ሰምተናል። ለጥሪው ጆሯቸውን የቆለፉበት አብይና የአብይ ድርጅት ብቻ ናቸው። ይህን ባለማድረጉ ለፖለቲካ ፍጆታ ሲባል በሴራ ፖለቲካ ያለ እድሜው መሞት የማይገባው ወጣት እንዲሞት ሆነ። በዛ የተነሳም ሌሎች በርካታ ንጹሃን ዜጎች እንዲሞቱ፣ እንዲቆስሉ፣ አገሪቱ ሌላ ቀውስ እንድታስተናግድ (እግዜር ይሁናትና!) ምክንያት ሆነ። ታድያ ማነው ለዚህ ተጠያቂው? ማን ነበር ይህን ማስቀረት ይችል የነበረው? በማን ውሳኔና እጅ ነበር?

አብይ፣ ሰልፊሽና የስልጣን ጥመኛ በመሆኑ ብቻ፣ አገሪቱን ከማቀራረብ ይልቅ፣ የባሰ ጽንፍ ነው ያስያዛት። ህወሓትን ሲታገሉ መቀራረብ ጀመረው የነበሩትን፣ ያራራቃቸውና ጽንፍ ያስያዛቸው የአብይ መንግስት ነው። ይህንን ቀዳዳ ተጠቅመው የውጭ ሃይሎች አገራችን ውስጥ ሴራ ቢሞክሩ እንኳን አይፈረድባቸውም። የሚያራርቅ እንጂ የሚያቀራርብ መሪና አሰራር እንደሌለን ይታወቃል። በድጋሚ ላንሳውና በድርድር ልዩነቱን ቀርፎ ቢሆን ኖሮ፣ የውጭ ሃይል አገራችንን የማተራመስ እድል ይኖረዋል? ግብጽ ብትሞክር እንኳን፣ መግባባት ካለ፣ በጋራ ያከሽፉት ነበር። ታዋቂ ሰው/ፖለቲከኛ ገድለው አመጽ ለመቀስቀስ ቢሞክሩ፣ ታዋቂ ሰዎች (ተፎካካሪዎች) በጋራ ቆመው፣ ተሰሚነታቸውን ተጠቅመው፣ ህዝባቸውን ያረጋጉ ነበር። አሁን ባለበት ሁኔታ ግን ይህ የሚቻል አልሆነም። ምክንያቱም ሁሉንም ነገር በራሱ መንገድ ብቻ ከማስተናገድ ውጭ ሌላ ነገር ስለማያውቅ።

ሲጠቃለል ከሀጫሉ ግድያ በስተጀርባ ያለው ሀይል ማንም ይሁን ማን፣ የመንግስት ተጠያቂነት ጎልቶ ይታየኛል። ገዳዮ ምንም ፖለቲካል ሞቲቭ የሌለው አንድ ተራ ሰው (ለምሳሌ የምኒሊክ አምላኪ) ሆኖ ቢገኝ እንኳን፣ አገሪቱን እዚህ ቀውስ ውስጥ የከተተው (ምናልባትም የከፋ ቀውስ ውስጥም ሊከታት የሚችለው) ማን በፈጠረው ችግር ምክንያት እንደሆነ ለሁላችንም ግልጽ ነው። ደጋግመን ድርድር፣ ውይይት፣ ድርድር፣ ስንል የነበረው ለዚህ ነው። አሁንም አገሪቱ ከዚህ ውጭ ሌላ መውጫ ቀዳዳ የላትም።

በመጨረሻ አንድ አቋሜን ግልጽ ላድርግ፣ ከሀጫሉ ግድያ በስተጀርባ የነጀዋር እጅ አለበት ብዬ የማላምነውን ያህል፣ የተደራጀ የአማራ ፖለቲከኞች ቡድንም ይኖራል ብዬ አላምንም። እነ ጀዋር አመጽ መቀስቀስ ከፈለጉ፣ ሀጫሉን መግደል አያስፈልጋቸውም። የአመንስቲ ሪፖርት የፈጠረውን አጋጣሚ ተጠቅመው ማቀጣጠል ይችሉ ነበር። ሀጫሉ ካስፈለጋቸውም አብሯቸው እንዲያቀጣጥል ማድረግ ይችሉ ነበር። እንዲህውም ነፍጠኛ የምትሏቸው የተደራጁ የአማራ ብሔርተኞችም ከዚህ ጀርባ አይኖሩም፣ ምክንያቱም የምኒሊክ ስም ከመጥፋት በላይ (ያውም ያልተለመደ አይደለም) የሚያሳስብ ዘርፈ ብዙ ችግር አለ። ለማይረባ ነገር ያን የመሰለ አርቲስት ገድሎ፣ የባሰ ጥፋትና ኪሳራ እንጂ ጥቅም እንደማይገኝ አያውቁም ለማለት አልደፍርም።

 

ሰ.ነ.

ወደ አምባገነናዊ ስርዓት መመለስ አገር ያሳጣል

ለዚህ  ጽሁፌ መነሻ ምክንያት ወደ ሆነኝ ነጥብ ልምጣና የኢህአዴግ አልጋ ወራሽ የሆነው ብልጽግና ልክ እንደትላንቱ ዛሬም በተመሳሳይ ጎዳና እየገሰገሰ ይገኛል። ኩንትራቱን ሊጨርስ እየተቃረበ ያለው ጠ/ሚ/ር አብይ አሕመድ፣ በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን ክፍፍል በአሸናፊነት ተወጥቶ ስልጣኑን ለማደላደል ሲል ብልጽግናን የመሰረተበት ሒደት፣ ድርጅቱን ለማጠናከርና አባላትን ለማፍራት እየተጓዘበትና ያለው መንገድ ከቀድሞ የኢህአዴግ ባህል ምንም የተለየ አይደለም። ኢህአዴግ የቀድሞ ስሙን ብቻ ቀይሮ በህይወት አለ። ልዩነቱ የቀድሞ ታጋዮች ኮትኩተው ባሳደጓቸው ካድሬዎች በፖለቲካ ጌም መሸነፋቸው ብቻ ነው። ሰዎቹ ተሸነፉ እንጂ የዘረጉት ባህል አልተሸነፈም። ካድሬዎቹ ከህወሓት ካድሬዎች ውጪ ቀሪዎቹ የነበሩት ናቸው። የሚተዳደሩት በለመዱትና በኖሩበት የድርጅት ባህል ብቻ ነው። ለዚህም ነው ብልጽግና ከኢህአዴግ የተለየ ባህል ሊኖረው የማይችለው።

ጠ/ሚ/ሩ በህዝብ ይሁንታ፣ በተሰጠው የሁለት አመት የስልጣን ገደብ ቀድሞ የገባውን ቃል አጥፎ፣ የዴሞክራሲ ተቋማትን ሳይገነባ፣ ነጻና ገለልተኛ ምርጫ ሳያካሒድ፣ ስልጣን በሰላማዊ መንገድ በህዝብ ለተመረጠ አሸናፊ ፓርቲ ማስተላለፍ የሚችልበትን እድል ሳይፈጥር፣ በማንኛውም መንገድ ስልጣን ላይ ለመቆየት የሚያስችሉትን አማራጮች እየዘረጋ ቆይቷል። አንዱ መንገድ የቀድሞ አጋሮቹን ገፍትሮ በአዲስና ታማኝ ካድሬዎች መተካት ነው። እኔ አሻግራችኋለው ከማለት ስልጣን ላይ ካልቆየሁ መታሰራችን ነው ወደ ማለት ተሸጋግሯል። ይህ አፍሪካ ነው፣ ምርጫ ማጭበርበር ብርቅ አይደለም ማለቱም ተሰምቷል። አንድ ሰሞን መተካከት የሚባል የፖለቲካ ዲስኩር ተፈጥሮ ነበረ። አቶ መለስ የቀድሞ ጓዶቹን በመተካካት አሰናብቶ፣ በአዲስ ሀይል ተካቸው። እኔም በቅቶኛል ስልጣን ለአዲሱ ትውልድ አስተላልፋለሁ ሲል ቆይቶ፣ ባለቀ ሰዓት ድርጅቴ መርጦ አዲስ አደራ ስለጣለብኝ፣ ግዴታዬን መወጣት አለብኝ አለ። በ99.96% አሸነፍኩ ብሎ የለየለት አምባገነን ሆኖ ብቅ አለ።

ዛሬም ዶ/ር አብይ እየተጓዘበት ያለው መንገድም ተመሳሳይ ነው። አሻግራለሁ ሲል ቆይቶ፣ ሌላ መሪ ማን አለ እስከማስባልና ዛሬ ስልጣን ላይ ካልቆየን መታሰራችን ነው የሚል አቋም እስከማራመድ ድረስ ዘልቋል።

ምርጫውን መራዘም አለበት የሚል ዘመቻ የተከፈተው አምና ነበር። ከተራዘመ የቅቡልነት ጥያቄ ሊነሳ እንደሚችል ሲገለጽ፣ ነሓሴ እንደሚካሔድ ተገለጸ። ውሳኔው ምርጫው በግፊት የሚራዘምበትን ሰበብ ለመፍጠር ያለመ ይመስል ነበር። የኮቪድ ወረርሽኝ ሲከሰት፣ ጥሩ አጋጣሚ ሆነለትና ምርጫው እንዲራዘም ተደረገ። ምርጫው መራዘሙ ብቻ ሳይሆን፣ ያልተገደበ ስልጣን የሚሰጠው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አሳወጀ። አዲስ የአፈና መርበብ ተዘረጋ። ስልጣን ላይ በጉልበት ለመቆየት ርብርቡ ቀጥሏል።

ይህ በዙርያው ላሰባሰባቸው ኪራይ ሰብሳቢዎች ትልቅ ሲሳይ ነው። ከህዝብ ተነጥሎ በካድሬና በድርጅቱ ሰዎት መተማመን ከጀመረ፣ መዝረፍ የፈለገ አሁን እንደልቡ ይዘርፋል። እንደድሮ በግፍ ራሱን ማዝናናት የሚያስፈልግ ካለም አሁን ያን ማድረግ ይችላል። ምክንያቱም ሰውዬው ከህዝብ ተነጥሏል። የሚፈራው ነገር እንዳይደርስበት ካድሬዎቹን ሸክፎ መያዝ አለበት። ሲሰርቁና ግፍ ሲፈጽሙ እየቀጣ ካድሬን ሸክፎ ማቆየት ደግሞ አይቻለውም። ስለሆነም ነጻ ይለቃቸው፣ ከቁጥጥሩ ውጭ ናቸው።

ትላንት በኮረና ስም፣ ትንሽ ሰብሰብ ያሉ ሰዎችን ለመበተን ሲባል፣ ወጣቶችን ገደሉ። እንደገና ቤት አፍርሰው ደግሞ በርካቶችን ለበሽታው ማጋለጣቸው አልቀረም። ከእንግዲህ እንዲህ አይነት ዝብርቅርቁ የወጣን ነገር ማስታረቅም፣ ማረምም አይቻለውም ጋሽ አጃግሬ። ያለው አማራጭ በስልጣኑ እስካልመጡበት ድረስ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ማለፍ ነው።

አብይ ብዙ ጊዜ ስቷል። አንኳር ስ ህተቶቹ ግ ን ሁለት ናቸው። አንደኛ ተቋማትን መገንባትና ራሳቸውን ችለው እንዲንቀሳቀሱ ማድረግ ሲገባው፣ እርሱን የሚያወድሱና በስልጣን ላይ ሊያቆዩት የሚሹ አጨብጫቢዎችን አፈራ። ሁለተኛ ስልጣን እየጣፈጠችው ስትሔድ ከህዝብ እየራቀ ሔደ፣ አምባገነናዊ ባህሪ እየተላበሰ ሔደ። አሁን መፍራት ጀመረ። ፍራቻው አገርን እንዳያሳጣን እፈራለሁ።

ሊበራላይዜሽን?መለስ ዜናዊ እና አብይ አሕመድ

መለስ ዜናዊን በብዙ ምክንያት እቃወመው ነበር። ይህን ከፋፋይ የዘር ፖለቲካ ማምጣቱ፣ ስልጣን ላይ ሙጭጭ ማለቱ፣ ስልጣን ላይ ለመቆየት የተጓዘበት ርቀት(የሚመራው ድርጅት በሀሳብ ድርቅ እስኪጠቃ ድረስ የተማረ ሰው የማያስጠጋ መሆኑ)፣ ወዘተ ሊጠቀሱ የሚችሉ ናቸው። ማንም የማይክደውና የሚደነቅበት ብቃት ደግሞ ነበረው። የኢኮኖሚክስ እውቀቱ ከባድ ሚዛን (ወርልድ ክላስ) ነበር።

መለስእነ ጆሴፍ ስቲግልዝ (በኢኮኖሚክስ ኖቤል ተሸላሚዎች) ፣ እነ ፒተር ጊልስ (አዋርድ ዊኒንግ ጋዜጠኞች)፣ እነ አሌክስ ዴ ቫል እና ሌሎችም ብዙ ግዜ መስክረውለታል። መጽሀፋቸው ላይ አንድ ምእራፍ ሙሉ ሰጥተው ትንታኔውን ከትበውታል፣ አድናቆታቸውን ችረውታል። መለስ የተደነቀበት የኢኮኖሚክስ እይታ “በድሀ አገር ሙሉ በሙሉ ነጻ ገበያ መፍቀድ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል”፣ “ሉአላዊነታቸውን ያሳጣቸዋል”፣ “በውጭ ባለሀብቶችና ኢንቨስተሮች ቁጥጥር ስር ይወድቃሉ” በሚለው አቋሙ ነው። በኢትዮጵያ ይህን ከምፈቅድ፣ እንደኤሊ ቀስ እያልን ብናዘግም እመርጣለሁ። የሚል ጽኑ አቋም ነበረው። በተለይ ጆሴፍ ስትግልዝ ከባንክና ከመሬት ሊበራላይዜሽን ጋር በተያያዘ በአንዲት ሌሊት ብዙና ጠንካራ የመከራከሪያ ጭብጦችን ማንሳቱ በአግራሞት ያወሳል። በተለይ ከኢስት ኤሽያ ክራይስስ ብዙ ምሳሌዎችን በመጥቀስ፣ ካገሩ ሁኔታ ጋር በማያያዝ አስደማሚ ክርክሮችን ማንሳቱን በአድናቆት መጽሀፉ ላይ ከትቦታል።

ዛሬ ሴንሲብል የሆኑ የአሜሪካ ምሁራን ጆሴፍ ስቲግልዝን ጨምሮ የነጭ ካፒታሊዝም ተቃዋሚዎች ናቸው። ዘ ኢኮኖሚስት በተደጋጋሚ የሚጽፋቸውን አርቲክሎች ላነበበ፣ የስካንዲኔቭያን ዓይነት ኢኮኖሚክ ሞዴል ተግባራዊ ለማድረግ የከጀሉ ይመስላል። በተደጋጋሚ በሚያስተዋውቁት አንድ የሽፋን ገጻቸው “ሶሻሊዝም የነገ ርእዮተ ዓለም” የሚል ምጸት ይዘው ቀርበዋል። የአየር ለውጥ የሚያሳስባቸው ኢኮኖሚስቶችና ፖለቲካል ሳይንቲስቶች፣ እንደዚሁም የአካባቢ ጥበቃ አድቮኬሲ ቡድኖችና ፈላስፋዎች እንደነ Naomi Klein ፣ Noam Chomsky፣ Slavoj Žižek እና የመሳሰሉት አለምን ለማዳን ከነጭ ካፒታሊስት (ነጻ ገበያ) ስርዓት መውጣት አለብን፣ ሲሉ ላንቃቸው እስኪነቃ ድረስ ያቀነቅናሉ።

በአንጻሩ አብይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመጣ ጀምሮ ማንም ሳይመርጠውና ይሁንታውን ሳይሰጠው፣ የኢትዮጵያን ህዝብና አገር ወክሎ የሚወስናቸው ውሳኔዎችና የሚፈጽማቸው ውሎች፣ እስከዛሬ ድረስ መለስና ኢህአዴግ አስከብረዉት የነበረ የኢኮኖሚ ሉአላዊነት የሚያስደፍር ነው። ይህ ድርጊቱ የአገሪቱን ሉአላዊነት በረጋግዶ አሳልፎ ከመስጠት ተለይቶ ሊታይ አይችልም። የአለም ካፒታሊስት ስርዓት አራማጅ ወደ መሀል እየመጣ ባለበት፣ በቅይጥ ኢኮኖሚ ስርዓት(ቅድሚያ ላገር ውስጥ ባለሀብት ቦታና ትኩረት በመስጠት) ኢኮኖሚያቸውን እያሳደጉ ያሉ አገራት በተበራከቱበት፣ አብይ ብቻውን ወደዚህ መንደር የሚያደርገው ግስጋሴ ከእንጭጭ ጭንቅላት የመነጨ ከሰራቸውና እየሰራቸው ካሉ ክፋቶች ሁሉ የከፋ ተግባር ነው።

አዎ ኢህአዴግ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ያስመዘገበው እድገት አለ። ከሚያገኘው ከፍተኛ ድጋፍና ብድር ጋር የማይመጣጠን ዝቅተኛ እድገት ቢሆንም የኢኮኖሚ ዕድገት ነበረ። ኢህአዴግ የሚወገዘው እድገት ባለማስመዝገቡ ሳይሆን፣ ህዝብን የዛ እድገት ተጠቃሚ አለማድረጉና የተመዘገበው እድገት ለጥቂቶች ብቻ የተደፋ ዳቦ በማድረጉ ነበረ። በሌላ አነጋገር በግልጽም ይሁን በድብቅ እየዘረፉ ራሳቸውንና በዙሪያቸው ያሉትን ብቻ እየጠቀሙ ሌላውን አድኽይተው ለመግዛት መሞከራቸው ነበር ትልቁና ዋነኛ ስህተታቸው። ይህን ስህተት አብይ በቀላሉ ማረም ይችል ነበር። ገበያውን በረጋግዶ ለውጭ ኮርፖሬሽኖች ልስጥ ማለት አያስፈልገውም ነበር።

ህዝብን የእድገቱ ተጠቃሚ ለማድረግና የተሻለ እድገት እንዲኖር ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበት አሰራር መዘርጋት ነበር የሚያስፈልገው። በሌላ አነጋገር በነጻ ገበያ ስም ያገር ሀብት ከመቸብቸብ በፊት የህግ የበላይነት ማስከበር መቅደም ነበረበት። ሙስኞችን ለህግ ማቅረብ፣ የህዝብ ንብረት ማስመለስ፣ ነጻ ሚድያ፣ ነጻ የፍትህና የኦዲት ስርዓት መዘርጋት ወዘተ በማስቀደም ህዝብን ተጠቃሚ ማድረግ መቅደም ነበረበት። በሒደት የአገር ውስጥ ባለሀብት አቅም ካካበተ ብኋላ እና ዛሬ ለውጭ ባለሀብት ሊበራላይዝ እየተደረጉ ያሉ የመንግስት ኩባንያዎችን በጨረታ ተወዳድሮ የማሸነፍና የመግዛት አቅም ሲፈጥር ነበር፣ ዛሬ እየተወሰደ ያለው የሪፎርም እርምጃ ሊወሰድ ይገባ የነበረው። በሌላ አነጋገር፣ ለአገር ውስጥ ባለሀብት ቅድሚያ በሚሰጥ ፕሮቴክሽኒስት ፖሊሲ ነው ነጻ ገበያ መለማመድ የሚኖርብን።

ከፈረሱ በፊት ጋሪው ቀድሟልና ወደ ተግባራዊነቱ ከመሸጋገሩ በፊት የሚመለከታቸው አካላት፣ ዩኒላተራሊ እየተወሰነ ባለው በዚህ ሰውዬ አካሔድ ላይ ልጓም ቢጤ ቢያኖሩለት ይመከራል።