, , , , ,

የኢትዮጵያ ጉዞ ወዴት? የኋላው ከሌለ የለም የፊቱ! (ክፍል 1)

  • የኢትዮጵያ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ተቋማት (institutions) በአንድ ወቅት ከአውሮፓ አገራት ጋር ተመሳሳይ ነበሩ። ኢትዮጵያ ከአውሮፓ አገራት ጋር ተነፃፃሪ ቦታ ላይ ነበረች።
  • በመቶዎች የሚቆጠሩ ማንነቶች ከስመው ጥቂት ወጥ የሆኑ ማህበረሰቦች ብቻ ዘመናዊቷን አውሮፓ መስረተዋል። አሁንም ግስጋሴው ወደ አንድነት ነው።
  • አውሮፓ የተከተለችው መንገድ ሌሎች በርካታ አገራት ተከትለውታል። ወይም ቀድመው ሄደውበታል (ለምሳሌ ቻይና)።  ኢትዬጵያ ይህን መንገድ አልተከተለችም። ለምን?
  • የኢትዮጵያ የተለየ መንገድ እንድምታው ምንድን ነው? እነዚህንና ሌሎች ነጥቦችን የሚዳስስ ጽሁፍ በሁለት ክፍል ተዘጋጅቷል። ክፍል አንድ እንሆ። መልካም ንባብ!

የአውሮፓ መንገድ

በመካከለኛው ዘመን አውሮፓ ከ500 በላይ በጎሳ በብሔርና በሌሎች ማንነቶች የተደራጁ ተቀናቃኝ “አገራት” (“መንግስታት”) እንደነበሯት ይነገራል። ከዛን ጊዜ ወዲህ ማዕከላዊ መንግስት ለመመስረትና አገራቱ አሁን የያዙትን ቅርፅ ለማስያዝ ስፍር ቁጥር የሌለው የውስጥና የውጭ ጦርነት ተካሂዷል። በነዚህ ጦርነቶች አንዱ አሸናፊ ጎሳ/ብሔር/አገር ሌላውን እየደፈጠጠና እያከሰመ፤ እሱም በተራው ሲሸነፍ በሌላው እየተደፈጠጠና እየከሰመ ዛሬ አውሮፓ የቆመችው 30 በማይሞሉ አገራት ብቻ ነው። ዝነኛው የፖለቲካል ሳይንስ ምሁሩ Francis Fukuyama በ2014 ባሳተመው Political Order and Political Decay በተሰኘው መፅሃፉ በተለይ በአውሮፓ የነበረውን የአገር ምስረታ ሂደት አስከፊ ገፅታውን እንዲህ ሲል አስቀምጦታል፥

”Any idea of a nation ineivitably implies the conversion or exlusion of individuals deemed to be outside its boundaries, and if they don´t want to do this peacefully, they have to be coerced [by states or by communal violence]. The twenty five or so nations that made up Europe at the middle of the twentieth century were the survivors of the five hundred or more political units that had existed there at the end of the middle ages.”

(እዚህ ላይ ፀሃፊው ”Any idea of a nation” ሲል የጀመረበት ምክንያት በቻይና በጃፓንና በሌሎች አገራትም የነበረው የአገር አመሰራረት ታሪክ ተመሳሳይ ስለነበረ ነው። ለበለጠ ግንዛቤ መፅሃፉን ማንበብ ይመከራል።)

የአውሮፓ አገራት በጊዜ ሂደት በባህል በቋንቋና በእምነት ከሞላ ጎደል ወጥ የሆነ ማህበረሰብ እየፈጠሩ፡ የማያሻማ ድንበርና ማዕከላዊ መንግስት በጉልበት እየመሰረቱ በመምጣት የአገር ግንባታቸውን ቀድመው አጠናቀው ዛሬ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት አስፍነው በስልጣኔ ጎዳና እየገሰገሱ ይገኛሉ።

ከዚህም አልፈው፡ አህጉሪቱን ወደ አንድ ታላቅ አገር (United States of Europe) የማሸጋገር ራዕይ ሰንቀው የጋራ ህበረት (European Union) በመፍጠር ላለፉት 7 አስርት ዓመታት ልዩነታቸውን በሚያጠብና አንድነታቸውን በሚገምድ ስራ ተጠምደው ቆይተዋል። በማንነት ፖለቲካ ግፊት ምክንያት በቅርቡ የተከሰተው የBREXIT ህዝበ ውሳኔ፡ ይህን ግብ ማሳካት ስለመቻላቸው ጥያቄ የሚያጭር ቢሆንም ራዕያቸውና ታሪካዊ አመጣጣቸው በጥቅሉ ሲታይ ወደ አንድነት ጎዳና የሚደረግ ያልተቋረጠ ጉዞ እንጂ የኃሊት የሚገሰግስ የመነጣጠል ጉዞ አለመሆኑን ያሳያል።

አገር በደምና ባጥንት የተገነባ የትውልዶች ርስት ነውና በእያንዳንዱ የአውሮፓ አገራት የሚኖሩ ዜጎች ከፋም ለማም የመጡበትን የታሪክ ጎዳና በፀጋ ተቀብለው፤ ካለፈው ስህተታቸው እየተማሩ ድንበር ተሻጋሪ የነገ መድረሻቸውን በጋራ ለማገንባት ተግተው ሲሰሩ ይታያሉ እንጂ ስለመጡበት መንገድ ሲነታረኩና አገራቱን እንዳዲስ አፍርሰው ለመገንባት ሲውተረተሩ አይታዩም። ምክንያቱም የኋላው ከሌለ የፊቱ እንደማይኖር ጠንቅቀው ያውቃሉ። የትላንቱን ጠባሳ መካስና መሻር የሚቻለው አገርን በጋራ ተረባርቦ በማበልፀግ እያንዳንዱን ዜጋ የብልፅግናው እኩል ተቋዳሽ በማድረግ ብቻ እንደሆነ ያውቃሉ። ዘላቂ ብልፅግና የሚኖረው ደግሞ የፖለቲካና የአስተሳሰብ ድንበሮችን አፍርሶ ልዩነትን በማጥበብ በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ጠንካራ እንድነት/ህብረት በመፍጠር መሆኑን ያምናሉ።

(ወደ ቀጣዩ ገፅ ተዛውሯል)

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *