, , , , ,

የኢትዮጵያ ጉዞ ወዴት? የኋላው ከሌለ የለም የፊቱ! (ክፍል 1)

የኢትዮጵያ መንገድ

በ17ኛው ክ/ዘመን ኢትዮጵያ የተከተለችው የተለየ መንገድ፡ ከአውሮፓ አገራት (ከኢንግሊዝ) የተለየ ዕጣፈንታ እንዲኖራት ኣድርጓል። በ1660ዎቹ ኢንግሊዝ የፊውዳል ስርዓት ገርስሳ የዘውዱን ስርዓት በመጠኑም ቢሆን የሚገድብ ፓርላመንታዊ ስርዓት ስትከተል፡ ኢትዮጵያ ለረዥም ዓመታት በእርስበርስ ጦርነት ስትታመስ ቆይታ በመጨረሻ ማዕከላዊው መንግስት የተዳከመበትና መሳፍንት የገነኑበት ዘመን ውስጥ ገባች። ለሁለት ክፍለዘመናት (16ኛውና 17ኛው ክፍለዘመን) በጦርነት በምትታመስበት ጊዜ እንኳን የተስፋ ጭላንጭሎች ነበሯት። ከማርቲን ሉተር ኪንግ የተሃድሶ ዘመን 30 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ የተሃድሶ እንቅስቃሴ በነ ደቂቀ እስጢፋኖስ ተጀምሮ እንደነበር ከፕሮፌሰር ጌታቸው ሃይሌ መጽሃፍ አንብበናል። እነ ፈላስፋው ዘርዓ-ያቆብ ያቆጠቆጡበት የጎንደር የ«cultural rennaisance» ዘመንም ቀላል የሚባል የለውጥ ጅማሬ አልነበረም። እነዚህ ጅምር እንቅስቃሴዎች ህዝቡ ውስጥ የዘለቁ አልነበሩምና ዘውዱን ሳይፈታተኑት ባጭሩ ተኮላሽተው ቀሩ። ነገር ግን የኢትዮጵያን ዕጣፈንታ እስከወዲያኛው የወሰነውን የፊውዳሎች ሹክቻን ማኮላሸት የቻለ ሃይል አልነበረም።

በ17ኛው ክ/ዘመን በኢንግሊዝ የፊውዳል ስርዓት ቀደም ብሎ ሊገረሰስ የቻለው ዘውዱን የሚፈታተን በግብር የተማረረ middle class ተፈጥሮ ስለነበር መሆኑን A&R ይገልጻሉ። በአንጻሩ ደግሞ በ18ኛው ክ/ዘመን በኢትዮጵያ ዘውዱን የተፈታተነው ሃይል ከፊውዳሊዝም ስርዓት ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ያለመ (በዘመኑ አጠራር ኪራይ ሰብሳቢ) የመሳፍንት መደብ ነበር። በመሆኑም ከድሮው የከፋ የጌታና የሎሌ (የባላባትና የጭሰኛ) ስርዓት በየመንደሩ ገነነ። ይህን ሁኔታ ቁጭት በሚያጭር መልኩ A&R በመጽሃፋቸው አሳጥረው አጠቃልለውታል፦

“The reason Ethiopia is where it is today is that, unlike in England, in Ethiopia absolutism persisted until the recent past. … Because of this Ethiopian society failed to take advantage of industrialization opportunities during the 19th and early 20th centuries.”

ቢሆንም ለበጎ ሆነ 

በ19ኛውና 20ኛው ክ/ዘመን አውሮፓ (ኢንግሊዝ) በኢንዱስትሪ የዕድገት ጎዳና ስትገሰግስ፡ ኢትዮጵያ በመሳፍንት የተዳከመውን ማዕከላዊ መንግስት በመመለስና “የተበታተነችውን” አገር በመሰብሰብ (reunification ) ስራ ላይ ተጠመደች። በአጼ ቴዎድሮስ የተጀመረው ኢትዮጵያን ወደ አንድ የማሰባሰቡና ጠንካራ ማዕከላዊ መንግስት የመመስረቱ ሂደት፡ በአጼ ዮሃንስ አራተኛ ቀጥሎ በዳግማዊ (አጼ) ምኒሊክ ተቋጨ። የዘመናዊቷ ኢትዮጵያ አባቶች አገሪቱን አንድ በማድረግ ሂደት በተጠመዱበት ዘመን፡ አውሮፓ ለኢንዲስቱሪዎቿ ፍጆታ የሚውል ጥሬ ዕቃ ፍለጋ አፍሪካን ለመቀራመት የሚያስችል እቅድ ነድፋ ተግባራዊ በማድረግ ዘመቻ ላይ ተጠምዳ ነበር።

ዳግማዊ ምኒሊክ አስቀድሞ ወደ ምስራቅና ደቡብ የአገሪቱ ክፍል ዘምቶ በጉልበት እያስገበረ ኢትዮጵያን ማቃናቱ፡ አገሪቱ ከዘመነ መሳፍንት በፊት እኩዮቿ በነበሩ አውሮፓውያን ቅኝ ገዢዎች ስር እንዳትወድቅ ረድቷታል። አጼ ምኒሊክ ከሁሉም የአገሪቱ አቅጣጫ ህዝቡን አሰባስቦ ወራሪውን የጣልያን ሃይል አድዋ ላይ ድባቅ በመምታት፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለቅኝ ገዢዎች ያልተበገረ ነጻነቱን በጉልበቱ የተጎናጸፈ ህዝብ አድርጎታል። ይኽም የዓለምን ፖለቲካ እስከወዲያኛው የቀየረ የጀግንነት ታሪክ ሆኖ ተመዝግቧል።

አድዋ ላይ አስደማሚ ታሪክ ባይሰራ ኖሮ ምናልባትም ቅኝ ግዛት ህጋዊነትን ተላብሶ (legitimate ሆኖ) በአፍሪካ ምድር ሊቆይ ይችል እንደነበር የታሪክ አጥኚው ረይሞንድ ዮናስ “The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire” በተሰኘው መጽሃፉ አስነብቦናል። ይህ ቢሆን ኖሮ ደግሞ ዛሬ የአፍሪካ ዕጣፈንታ እንደ ሰሜን አሜሪካና አውስትራሊያ በወራሪ ሰፋሪዎች ብቻ የቆመች አህጉር ልትሆን ትችል ነበር ማለት ነው። ወደ አሜሪካና አውስትራሊያ የሄዱ የቀድሞ የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ኗሪዎቹን (native Idians and Aborginal Australians) አክስመው እዛው በመስፈር አገራቱን መመስረታቸው ልብ ይሏል። ይህ ግን በአፍሪካ አልሆነም። ምክንያቱም ኢትዮጵያ እንደዘመነ መሳፍንቱ ጊዜ ተበታትና አልጠበቀቻቸውም። አንድ አገርና በአንድ ንጉስ ስር የሚተዳደር ህዝብ የነበራት “ጠንካራ” አገር ሆና ስለቆየቻቸው ቅኝ ገዢዎችን መመከት የቻለች የዓለማችን ብቸኛ አገር ልትሆን ችላለች። በሌላው ዓለም የሚገኝ ጭቁን የሰው ዘር በሙሉ ይኽንን ድል አይቶ ለገዢዎች የሚመች ቄጤማ መሆን አልቻለም። ተገዢው ብቻ ሳይሆን ገዢውም፤ የሰው ዘር በሙሉ እኩል መሆኑን አምኖ ለመቀበል ተገደደ። የዓለም ታሪክ፡ የዓለም ፖለቲካ እስከወዲያኛው ተቀየረ። የሆነው ቢሆንም ለበጎ ሆነ!

(ይቀጥላል)

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *